የደብረ ብርሃን ቅዱስ ባስልዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በሸዋሮቢት ከተማ ትምህርት ሊጀምር መሆኑን አበሠረ።
ሐምሌ ፲፭ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም (አቡቀለምሲስ ሚዲያ ፤ ደብረ ብርሃን) የደብረ ብርሃን ቅዱስ ባስልዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በ2019 ዓ.ም የትምህርት ዘመን በሸዋሮቢት ከተማ ቅዳሜ እና እሁድ በኤክስቴንሽን ትምህርት ለማስተማር መዘጋጀቱን አብሥሯል። ይህ የምሥራች ይፋ የተደረገው የኮሌጁ ከፍተኛ አመራሮች ከሸዋሮቢትና ከቀወት ወረዳ ቤተ ክህነት የሥራ ሓላፊዎች እና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ባካሔዱት ውይይት መሆኑ ተገልጿል። በዕለቱ በስፋት ማብራሪያ የሰጡት የኮሌጁ አመራሮች፡-ዶክተር አቤሴሎም ነቅዐጥበብ፦የቅዱስ ባስልዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዋና ዲን፣ ሊቀ አእላፍ ዮርዳኖስ አቢ፦ የቅዱስ ባስልዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ምክትል ዲን፣ ሊቀ ልሳናት ደበበ ፍልቄ፦የቅዱስ ባስልዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ አካዳሚክ ዲን ናቸው። አመራሮቹ በገለጻቸው ኮሌጁ የሚያስተምራቸውን የትምህርት መስኮች እና የትምህርት አሰጣጥ ሂደቶችን አብራርተዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች ለአካባቢው ቅድሚያ በመስጠት ለተደረገላቸው መልካም እድል ለሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስን የላቀ ምስጋና አቅርበዋል። በተመሳሳይ ቅዱስ ባስልዮስ መንፈሳዊ ኮሌጅ አመራሮች ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን፣ ለቀጣዩ የትምህርት ዘመን ስኬትም የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። በውይይቱ ላይ የሸዋሮቢት ከተማ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ የቀወት ወረዳ ቤተ ክህነት እንዲሁም የአጎራባች ወረዳዎች ካህናት፣ ዲያቆናት፣ መዘምራን እና የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች ተሳትፈዋል ሲል የዘገበው ሸዋሮቢት ከተማ ቤተ ክህነቱ ሚዲያ ነው።